Wednesday, August 13, 2014

የሮዝ አሳታሚ ድርጅት ሥራ አስኪያጅ አቶ እንዳልካቸው ተስፋዬን ፣ ኢብራሃም ሻፊ፣ እንዳለ ተሺና ሀብታሙ ሥዩም ከአገር መሰደዳቸውን ተሰማ፡፡

የአዲስ ጉዳይ መጽሔት አዘጋጆች ከአገር መሰደዳቸው

-ዓቃቤ ሕግ ክስ ሊመሠርት ነው
10570542_10204024912521089_4618968976545930065_n 
በሮዝ አሳታሚ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር አማካይነት ከኅዳር 1999 ዓ.ም. ጀምሮ ሲታተም የቆየው ‹አዲስ ጉዳይ› መጽሔት አዘጋጆች ከአገር መሰደዳቸው ተሰማ፡፡
የተለያዩ ማኅበራዊ ድረ ገጾች የአዲስ ጉዳይ መጽሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተርና የሮዝ አሳታሚ ድርጅት ሥራ አስኪያጅ አቶ እንዳልካቸው ተስፋዬን ጨምሮ የመጽሔቱ ምክትል ዋና አዘጋጅ ኢብራሃም ሻፊ፣ ከፍተኛ አዘጋጅ እንዳለ ተሺና የመጽሔቱ ዓምደኛ ሀብታሙ ሥዩም ከአገር መሰደዳቸውን ዘግበዋል፡፡
በቅርቡ ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለመናድና ሕዝቡ በመንግሥት ላይ ያላግባብ አመኔታ እንዲያጣ አድርገዋል በማለት የፍትሕ ሚኒስቴር ክስ እንደሚመሠረትባቸው ካስታወቀው አምስት መጽሔቶችና አንድ ጋዜጣ መካከል አዲስ ጉዳይ መጽሔትም መካተቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ የፍትሕ ሚኒስቴር መግለጫ የመንግሥትን ቻይነትና ትዕግሥት ከመጤፍ ባለመቁጠር የሚፈጽሙትን የሕግ ጥሰት አባብሰው በመቀጠላቸው፣ የአገሪቱ ሕግ በሚደነግገው መሠረት የወንጀል ክስ መመሥረቱን አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅትና የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት በታኅሳስ ወር 2006 ዓ.ም. ‹‹ሰባት መጽሔቶች በተከታታይ ሕትመቶቻቸው በአሉታና በተደጋጋሚ ያነሷቸው ጉዳዮች የአዝማሚያ ትንተና›› በሚል ርዕስ፣ በተመረጡ መጽሔቶች ላይ ከመስከረም 1 ቀን 2006 ዓ.ም. እስከ ኅዳር 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ድረስ ያሉ ሕትመቶች ላይ የዳሰሳ ጥናት አድርገው የጥናቱን ዋና ዋና ግኝቶች አውጥተው ነበር፡፡
በወቅቱ በወጣው ጥናት ዋና ዋና ግኝቶች መካከል የመንግሥትን ኃላፊዎችን የግል ሰብዕና የሚነኩ፣ የአመፃ ጥሪዎችን የሚጠሩ፣ የኢኮኖሚ ዕድገቱን የሚክዱና ሕገ መንግሥትን የሚያጣጥሉ ጽሑፎችን ማተም የሚል ሲሆን፣ አዲስ ጉዳይ መጽሔትም ከተዘረዘሩት የጥናቱ ግኝቶች በርከት ያሉትን አስተናግዷል፡፡ በማለት የአዝማሚያ ጥናቱን ገልጾ ነበር፡፡
የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን የሕትመት ሚዲያዎች የሰኔ ወር 2006 ዓ.ም. አማካይ የኅትመት ሚዲያዎች ብዛት በድረ ገጹ ላይ ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ በዚህም መሠረት አዲስ ጉዳይ 11,750 ኮፒ ማሰራጨቱን ይገልጻል፡፡ ከመጽሔቱ ባልደረቦች የመረጃውን ትክክለኝነት ለማጣራት ተደጋጋሚ ጥረት ቢደረግም የሞባይል ስልካቸው ዝግ በመሆኑ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ ፍትሕ ሚኒስቴር እከሳቸዋለሁ ባላቸው አምስት መጽሔቶችና አንድ ጋዜጣ ላይ ነሐሴ 7 ቀን 2006 ዓ.ም.፣ ዓቃቤ ሕግ ክስ እንደሚመሠርት ለማወቅ ተችሏል፡፡

No comments:

Post a Comment